ከዛሬ ስድስት ወር በፊት ወፍራሙ መንግስታችን ተጭኗት “ህልፈተ ህይወት አደረገች” ብለን አዝነን ለቅሶ ተቀምጠንላት የነበረችው አውራምባ ታይምስ ጋዜጣ “እጅ መስጠት የለም ብላ” (ትንሽ እናጋነው ካልድ ደግሞ መቃብሯን ፈንቅላ) በዌብ ሳይት በኩል መምጣቷን ትላት ይፋ አደረገች።
አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች እንደሚሉት “መንግስታችን እኔ ብቻ ላውራ እናንት ዝም በሉ” በሚል እንድተዘጋ ያደረጋት፤ ተወዳጇ አውራምባ ታይምስ ጋዜጣ በኢትዮጵያ ሰማይ ስር ዘወትር ቅዳሜ ነግሳ ትውል ነበር። ጋዜጣዋ ከመዘጋቷ ከአመት በፊት ማኔጂንግ ኤዲተሯ ዳዊት ከበደ ሲፒጄ ከተባለው ለጋዜጠኞች የቆመ ድርጅት “እሰይ አበጀህ የኛ ልጅ” ተብሎ በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የመጣው ይምጣ ብለው ለሚሰሩ ጋዜጠኞች የሚሰጠውን ሽልማት ተበርክቶለት ነበር።
ትላትን በዋሽንግተን ዲሲ (የሆቴሉን ስም ረሳሁት) ብቻ በአንድ ሆቴል በተደረገው የመክፈቻ ስነስርዓት ላይ አክቲቪስት እና አርቲስት ታማኝ በየነን ጨምሮ በርካታ እንግዶች በመድረኩ ላይ የተገኙ ሲሆን በቪዲዮ እና በስካይፒም የሲፒጂ አፍሪካ አስተባባሪ መሃመድ ኬታ የአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ ሊቀመንበር አቶ ኦባንግ ሜቶ እና ሌሎችም ግለሰቦች ስለ አውራምባ ታይምስ ዌብሳት መጀመር የተሰማቸውን ደስታ ገልጠዋል። (በቅንፍ አንዳንድ ግለሰቦች የተባልኩት እኔ መሆኔን አሳብቃለሁ!)
አውራምባ ታይምስ በአገርቤት ዘጋቢዎቿ እየታገዘች ስለ ኢትዮጵያ የተለያዩ ዘገባዎችን ለማቅረብ ቆርጣ የተነሳች መሆኗን ዳዊት ከበደ ነግሮኛል።
አውራምባ ታይምስን ለመጎብኘት ተነሳሽነት ያላችሁ ግለሰቦች እና ድርጅቶች http://www.awrambatimes.com/ ብላችሁ እንደምታገኟት ዜናን በጨዋታችን ሊነግራችሁ ይወዳል!
[…] ይህችን ጠቅ በማድረግ ያንብቡት:: ስለ ርእዮት ከተጻፉት ደግሞ የአቤ ቶኪቻውን ያዙልኝ አቤ ዜናውም ትንተናውም እንግዲህ በጫወታ መልክ […]