ዛሬ አዲሳባ ፍትህ ጋዜጣ ላይ የምትወጣ ስለ አቶ መለስ መጥፋት አበክራ የምትጠይቅ እና የምትጨነቅ አንድ ጨዋታ አለችኝ። ለዝች ብሎግ አንባቢዎች ነገ ትለጠፋለች። እስከዛ ይቺን መቆያ እንኩማ፤

ያው ሁላችንም እንደሰማነው አቶ መለስ ተይዘዋል። ስንቱን ሲይዙ የነበሩት ሰውዬ አሁን ግን ራሳቸው በእግዜሩ በሽታ ተይዘዋል። በህመማቸው ሳቢያም ፓርላማው እንኳ ይኸው የ2005 ዓ.ም በጀቱን እስካሁን አላፀደቀም።

እኔ የምለው ግን በቃ አቶ መለስ ከሌሉ ሁሉም ነገር አለቀለት ማለት ነው? የምር ይሄ ነገር በጣም ያሳስባል።

ልክ እንደ አቶ መለስ ሆኖ የሚጫወት “ካስት” እንዴት አይኖርም!? እሳቸው ስለታመሙ እከሌ ወይም እከሊት እንደ አቶ መለስ ሆነው ይጫወቱልናል! መባል የለበትም እንዴ!? የቡድን ስራ ምናምን የሚባል ነገር የለም ማለት ነው…? አይበልባቸውና የሆነ ነገር ቢሆኑ ታድያ ምን ሊውጠን ነው!

ለማንኛውም ይቺን ያኽል ከተንደረደርን ወደ ፉገራችን እንግባ፤

እንግዲህ ይህ ዘገባ የሚተላለፍላችሁ በእግዜር ቁጥጥር ስር በሚገኘው ቴሌቪዥን ነው አሉ። በእግዜር ቁጥጥር ስር የሚገኝ ቴሌቪዥን የቱ ነው? ካሉኝ ህልም መሆኑን እገልፃለሁ። የምር ግን እግዜር ህልምን ያህል ቴሌቪዥን በእያንዳንዳችን ላይ ገጥሞ ሳለ ለገዛ ፕሮፖጋንዳው መጠቀም ሲችል በነፃነት የፈለገንን እንድናይ ማድርጉ ምን ያህል ዲሞክራት ቢሆን ነው ብለው አይደነቁም! በእውነቱ እንደ እግዜር አይነት ነፃነት የሚሰጠንን መንግስት ያምጣልን! እንደርሱ እንኳ የትም አይገኝም ግን ቢያንስ የሚቀራረብ…

ለማንኛውም እግዜር ኢህአዴግ አይደለም እንጂ ቢሆን ኖሮ የአቶ መለስን መያዝ አስመልክቶ በቴሌቪዥኑ እንዲህ ይል ነበር፤ ብለን ብንገምት ምን ይለናል!? በነገራችን ላይ ይህ ዜና ቃል በቃል ከዚህ በፊት እነ እስክንድር ነጋ፣ እነ አንዳለም አራጌ፣ እነ ውብሸት እና ርዮት የተያዙ ጊዜ ኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ያነበበልን ነው። ልዩነቱ እነ አስክንድርን የያዛቸው ፖሊስ ነው አቶ መለስን ደግሞ በሽታ ነው፤

አባቴ በህመም አይቀለድም ይለኝ ነበር። ነገር ግን በላዬ ላይ ያደረው በል ብሎኛልና እንደሚከተለው እጀምራለሁ፤ አባቴ ይቅርታ አድርግልኝ። እርስዎም ሲጀምሩ እግዜሩ ይቅር ይበልህ ብለው ከጀምሩልኝ ችግር የለውም!

ገመትን፤
አቶ መለስ ዜናዊ ራሱን ኢህአዴግ ብሎ ከሚጠራ አሸባሪ ድርጅት ጋር የህዝብን መሰረተ አንድነት እና የሀይማኖት አውታሮችን ለማፈራረስ ሲንቀሳቀሱ በህብረተሰቡ ጥቆማ እና በፌደራል በሽታ እና ፀረ ሽብር ወቅስፈት ግብረ አይል በቁጥጥር ስር ውለዋል።

ግለሰቡ በውጪ ሀገር የሚንቀሳቀሰው ቻይና ኮሚኒስት የተባለ አፋኝ ድርጅት የሀገር ውስጥ አደራጅ፣ ቀስቃሽ እና አንቀሳቃሽ ከመሆናቸውም በተጨማሪ ስልጣንን ሽፋን በማድረግ አብዮታዊ ዴሞክራሲ አክራሪነት እንዲስፋፋ፣  አንድ ለአምስት የሚል ህዋስ በመፍጠር በመላው ሃገሪቱ መረብ ዘርግተው ሀገሪቱ ላይ ከፍተኛ የሆነ የሽብር ጥፋት ለመፈፀም ሲንቀሳቀሱ እንደነበር ታውቋል።

ተጠርጣሪው ግለሰብ በልማት ስም ሰላማዊ የሀይማኖት ሰዎችን ከፀሎት ስፍራቸው በማፈናቀል እንዲሁም ህገ መንግስቱን ሽፋን በማድረግ በርካታ ሙስሊሞችን ኢላማ ያደረገ ጥቃት ሲፈፅሙ እንደነበር ፌደራል በሽታ እና ፀረ ሽብር ወቅስፈት ቡድን አረጋግጧል።

ተከሳሹ በቁጥጥር ስር ሲውሉ ህመሞቹ የመያዣ ፈቃድ እንዳሳዩዋቸው እና በአሁኑ ሰዓት በተኙበት ቦታ የተለያዩ በሽታዎች በጥበቃ ስር ያሉ ሰዎች ማግኘት ያለባቸውን ተገቢ እንክብካቤ እያደረጉለት መሆኑን ተጠርጣሪው ራሳቸው አረጋግጠዋል!

አቶ መለስ ዜናዊ በአሁኑ ሰዓት የተያዙ ሰዎች መብት እንዲያገኙ መደረጉን ለማረጋገጥ የተለያዩ ጎብኚዎች እንዲመለከቷቸው ተፈቀዷል። ጎብኚዎቹም ተጠርጣሪው እንደፈለጉ ማቃሰት እና የሚያስፈልጋቸውን ነገርም ያለ አንዳች ገደብ ሲጠይቁ መመልከታቸውን ተናግረዋል።

የተጠርጣሪው ግለሰብ ፍርድ ነፃ እና ገለልተኛ በሆነው መንግስተ ሰማያት መታየት የተጀመረ ሲሆን ጥፋታቸውን አምነው እና ተፀፅተው ይቅርታ ከጠየቁ ምህረት ሊደረግላቸው እንደሚችል ተያይዞ የደረሰን ዜና ያመለክታል።
በድጋሚ ይቅር ይበለን ዜናው አበቃ!

About abetokichaw

ራሱን አቤ ቶኪቻው እያለ የሚጠራ አንድ ግለሰብ በአዲሳባ ከተማ ይኖር ነበረ። በአዲሳባ ከተማ በሚኖርበት ግዜ የመንግስትን ያልተስተካከለ አስራር ሲያሽሟጥጥ መንግስት ተቀየመው። ምን መቀየም ብቻ… ከሀገር እንዲሰደድ ሁሉ አደረገው እንጂ! ይህ ግለሰብ… ከዚህ በፊት ሁለት ሽሙጣዊ መፅሐፍትን ያሳተመ ሲሆን “የአቤ ቶኪቻው ሽሙጦች” እና “ስላቆች” ይሰኛሉ። አሁንም ቢሆን የማይሆን ነገር ካየሁ ከማሽሟጠጥ አልመለስም የሚለው ይህ ስደተኛ… እነሆ በዚህ ብሎግ ላይ ደግሞ በሽሙጥ የአፃፃፍ ብልሃት ቢያንስ በሳምንት አንድ ግዜ ልከሰት ብሎ “ሀ” ብሏል።

3 responses »

  1. በለው! says:

    “ለምሁሩ እኔ ልነጠፍለት አለች አሉ ኮብላይ እስቶን” !
    “ይህ እየተንጋደዱ ፎቶ መነሳት የፓረቲው መለያ ነው ? የብአዴኑ በረከት ወደ ግራ ሲያዘምሙ ከህወአት አቶ ለገሠ(መለሰ) ወደ ቀኝ የፓረቲያቸውን የረጅም ዱላ ቅብብል በቆረጣ ሲሾፉ ከተነሱት የተወሰደ! እሩቅ አሳቢ ብራስለስ አዳሪ አሉ…!
    ስሞኑን ብዙ የተዘጉ በርካታ የተከፈቱ የኢትዮጵያ የአፍሪካና የፌዴራሉ ዋና ከተማ ላይ ክስተቶች ነበሩ፤ጠ/ሚ ከላይ በቀረበባቸው መገለጫ ሁኔታዎች እስኪስተካከሉ ድረስ ለጊዜው ለጥያቄ ካረፉበት ቦታ ሆነው የሀገሪቱን የ፪፼፭ ዓ.ም ባጀት በእሰካይብ ለፓርላማ የቅርብ አድናቂዎቻቸው ባስተላለፉት የአፅድቁት መልዕክት በአንድ ድምፀ ታቅቦ ማለትም በእሳቸው ያለመገኘት ብቻ በሙሉ ጭብጨባ እና የፉገራ ሀሳብ ፀደቀ እልልልልልልልል….!

    “አቶ መለስ ዜናዊ ራሱን ኢህአዴግ ብሎ ከሚጠራ አሸባሪ ድርጅት ጋር… እንደ ፀጉር እና ማበጠሪያ ባላቸው ቁርኝት የአካባቢውን ቀጠና የሽብርተኞችን አሰራር ሙሉ ልምድ ያላቸው መሆኑ ቢታመንም የሱዳኑ አልበሽር ምስክሬ ነው አብረን ብዙ ጊዜ ያሳለፈኩት በኤርትራ ዋሻ ስለሆነ የቅርብ ወዳጄ የሩቅ አናዳጄ ኢሳያስም ያውቅልኛል ብለዋል።

    “ስልጣንን ሽፋን በማድረግ አብዮታዊ ዴሞክራሲ አክራሪነት እንዲስፋፋ፣ አንድ ለአምስት የሚል ህዋስ በመፍጠር በመላው ሃገሪቱ መረብ ዘርግተው ሀገሪቱ ላይ ከፍተኛ የሆነ የሽብር ጥፋት ሕዝብ በዘር፣ በጎሳ፣በሃይማኖት፣ በብሔር፣በክክል፣ በቋንቋ፣ ተለያይቶ እርስ በእርሱ እንዲፋጅ, ባይነቁራኛ እንዲተያይ, አንዱ በአንዱ ላይ እንዲነሳ፣ የውሸት ታሪክ መጽሀፍ በማሳተም, ለሀገር የሚጠቅሙ ጋዜጠኞችን, ምሁራንን ከሀገር በማሳደድ፣ በማሰር፣ ሀገርን የራሳቸው የግል ንብረት አድርገው ‘ሀገር በላ’ ከሚሉት ደርግ በከፋ መልኩ ዜጋን አፈናቅለው “የሩዝ አብዮትን” ለመገንባት ከቻይና እና ከሕንድ ያለኝ ወዳጅነት ከመቼውም በበለጠ እስከ ደም ጠብታ ይላሉ። ደርግ ሳይበላ ሳያስበላ መሬትን ይዞ ጫካ አስበላው ሲሉ… ኢህአዴግ ከራሱ ተርፎ ቻይና፣ሕንድ፤አረብንም አጠገበው ብለው መከላከያቸውን አቅርበዋል።(ሕዝብ ሦስቴ አይበላም የምግብ ዕጥረትአለ!)

    “የተሟላው የክስ መዝገብ ተጠናቆ ለፍርድ ቤቱ እስኪቀርብ ድረስ ግለሰቡ የተጠየቁትን ትተው ያልተጠየቁትን መመለስ ያሸሹኛል ይደብቁኛል ብለው የተማመኗቸው ቢኖሩም የማያስጥሏቸው መሆኑን ተረድተው በክስ መዝገቡ ላይ እንደተጠቆመው ባረፉበት ሆስፒታል “የኢትዮጵያ አምባሳደር ወጥ ቤት…”አበበ አስረስ ዜናዊ ” በሚል የክልል መታወቂያ
    አሳይተዋል በቁጥጥር ስር ሲውሉ ህመሞቹ የመያዣ ፈቃድ እንዳሳዩዋቸው እና በአሁኑ ሰዓት በተኙበት ቦታ የተለያዩ በሽታዎች በጥበቃ ስር ያሉ ሰዎች ማግኘት ያለባቸውን ተገቢ እንክብካቤ እያደረጉለት ጎብኚዎቹም ተጠርጣሪው እንደፈለጉ ማቃሰት እና የሚያስፈልጋቸውን ነገርም የመፃፍ፣ የማንበብ፣ የመናገር፣ የመጠየቅ፣የመፀለይ ፣ሚዲያን ያለገደብ የመጠቀም
    ሙሉ መብታቸው ተጠበቆ ነፃ እና ገለልተኛ በሆነው መንግስተ ሰማያት መታየት የፍርድ ሂደት የተጀመረ ሲሆን ጥፋታቸውን አምነው እና ተፀፅተው ይቅርታ ከጠየቁ ምህረት ሊደረግላቸው እንደሚችል ተረጋግጧል። ከማራቸውም ይማራቸው! እንደሥራቸው ይፈረድባቸው! በድጋሚ ይቅር ካላቸው ይቅር ይበላቸው!አያስቀርቅራቸው ቀና አርጋቸው!!!

  2. meretwork says:

    I have seen the wicked a tyrant”Andspreading himself as a luxuriant tree in native soil”And yet he proceeded to pass away and there he was not”And I keep seeking him and he was not found”And the salvation of the righteous ones ts from God”He is their fortress in the time distress”For the very arms of the wicked ones will be broken! Amen!
    Ps-37-35-39

  3. Mignot says:

    abe tefah beselam new?

Leave a comment