ዛሬ ከጠዋቱ አንድ ሰዓት ተኩል አካባቢ በአዲስ አበባ ፀሐይ ስር ቬነስ የተባለችው ፕላኔት ስታቋርጥ ለ18 ዲቂቃዎች እንደምትታይ መሰለ ገብረ ህይወት የተባለው የኢቲቪ ዜና አንባቢ ትላንት ማታ በፈገግታ እና በታላቅ ድል ስሜት ታጅቦ ነገሮናል። ከፈገግታውና ከአነጋገሩ እንደተረዳሁት ከሆነ ነገ ይህንኑ ዜና ምን ብሎ ሊነግረን እንደሚችል እንደሚከተለው እገምታለሁ…

ቬነስ ፕላኔት በአዲስ አበባ ሰማይ ስር ማለፏ ያስመዘገብነው ልማት ውጤት መሆኑ፤ የተለያዩ ባለስልጣናትን አነጋግሮ የዘገበው ዋልታ ኢንፎርሜሽን ማዕከል ፕላኔቷ በ18 ደቂቃ ቆይታዋ በአገሪቱ መልካም አስተዳደር እና ዴሞክራሲ ሰፍኖ መመልከቷን አያይዞ ዘገቧል።
ለዝርዝሩ… (“ትልና…” አሉ የዞን 9 ልጆች አንዳቸው ወይም ሁለታቸው…! (እዝችጋ አንድ ማስታወቂያ ተናግሬ እቀጥላለሁ ዞን 9 የተባለ ብሎግ መከፈቱን ሰምታችሁ ይሆን?  ወደ አስር የሚጠጉ “ጦማሪያን” በአንድ ላይ በመሆን የከፈቱት ይህ “ጦማር” “ስለሚያገባን እንጦምራለን!” በሚል መሪ ቃል የተከፈተ እንደሆነ አናቱ ላይ የተፃፈውን አይቼ ተረድቻለሁ… ጎራ ብላችሁ ብታዩት አሪፍ አሪፍ “ጡመራ” እንደሚኖር ድንጋይ ነክሼ እመሰክራለሁ…!)   ይኸው መግቢያው!

ወደ ዜናችን ስንመለስ…

የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር አቶ ኃይለማሪያም ደሳለኝ እንደገለፁት “አሁን ሀገራችን ከምዕራብ ሀገራት እና ከቻይና በተጨማሪ ከቬነስ ፕላኔት ጋር ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ማድረግ ጀምራለች” ካሉ በኋላ፤ “ቬነስ ከሌሎች ሀገራት በሙሉ እኛን መምረጧ ያለን ልማታዊ ተሳትፎ ከፍተኛ በመሆኑ እንደሆነ ግልፅ ነው” ሲሉ ተናግረዋል። አቶ ኃይለማሪያም አያይዘውም፤ “በአሁኑ ወቅት ከአለም ሀገራት በተጨማሪ ሌሎች ፕላኔቶችም ሀገራችን እየተከተለች ያለችው የልማትና ዴሞክራሲ አቅጣጫ ትክክል መሆኑን አምነው የተቀበሉበት ሁኔታ ነው ያለው” ሲሉ ለዘጋቢያችን ገልፀውለታል።

ቬነስ እንዲህ ነበር የታየችው  ብሎ ቶማስ ገብሬ የተባለ የፌስ ቡክ ወዳጃችን ከለጠፈው ላይ የተወሰደ! ቶማስን እግዜር ይሰጠው ብለን እንመርቃለን!

የብሄራዊ መረጃና ደህንነት ባለስልጣንና የፌደራል ፖሊስ የጋራ ጸረ ሽብር ግብረ ኃይል እንዲሁም የመከላከያ ቃል አቀባዮች  በበኩላቸው ባስተላለፉት መልዕክት፤ “በአገራችን ያለው አስተማማኝ ፀጥታ ቬነስ በአዲሳባ ፀሀይ ስር ማቋረጥን እንድትመርጥ አድርገዋታል” ያሉ ሲሆን፤
“ለፕላኔቷ ስጋት ይሆናሉ ተብለው የታሰቡ የሻቢያ ተላላኪ ፀረ ሰላም ኃይሎች በህብረተሰቡ ጥቆማ ቀድመው በቁጥጥር ስር በመዋላቸው ያለ አንዳች ችግር ፕላኔቷ በሰላም ከተማችንን ለማቋረጥ አስችሏታል።” ብለዋል። አክለውም፤ “ፀረ ሰላም ሀይሎቹ ባይከሽፍባቸው ኖሮ በከተማው ውስጥ ሁከት እና ብጥብጥ በማስነሳት ፕላኔቷ የምታደርገውን ጉዞ ለማጨናገፍ እና የሀገሪቱን መልካም ስም ለማጠልሸት አስበው እንደነበር ገልፀዋል።

የአዲሳባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ኩማ ደመቅሳ በበኩላቸው ቬነስ በአዲስ አበባ ከተማ ፀሀይ ስር ባደረገችው የአስራ ስምንት ደቂቃ ቆይታ የከተማዋን እድገት እንዳደነቀች በተለይም ወጣቶች በጥቃቅን እና አነስተኛ ተደራጅተው እየሰሩ ያሉት የኮብል ስቶን የመንገድ ንጣፍ በጣም እንደማረካት ገልፀው በእርሷ ከተማ እንዲህ አይነት ነገር እንዲለመድ ልምድ መቅሰሟንም አስረድተዋል።

ቬነስ ፕላኔትን ባነጋገርናት ወቅት በአዲስ አበባ ከተማ በተመለከትችው በሙሉ እንደተደነቀች እና በመቶ አመት ውስጥ በርካታ ለውጦችን መመልከቷን የገለፀች ሲሆን፤ አዲስ አበባ በዴሞክራሲ እና በመልካም አስተዳደር የተሳካላት ከተማ መሆኗን እንዳስተዋለች በአድናቆት ገልፃ፤ ያየችውን በሙሉ ለሌሎች ፕላኔቶች እንደምትነግር እና እርሷም ከእንግዲህ ቶሎ ቶሎ ብቅ እያለች ማራኪዋን እና ልማታዊዋን ከተማ እንደምትጎበኝ ገልፃለች!

ዜናው በዚህ አበቃ….(ለጥ ብሎ ጠረቤዛ ስሞ ሊሰናበት ነበር ለካስ መሰለ ገብረ ህይወት ወፍራሙ ሰውዬ ነው!) ከወፈሩ ዜና አይፈሩ… እንበለው ይሆን…? (ይቺ እንኳ ጨዋታ ናት መሴ… ግን አናጋን እሺ!)

About abetokichaw

ራሱን አቤ ቶኪቻው እያለ የሚጠራ አንድ ግለሰብ በአዲሳባ ከተማ ይኖር ነበረ። በአዲሳባ ከተማ በሚኖርበት ግዜ የመንግስትን ያልተስተካከለ አስራር ሲያሽሟጥጥ መንግስት ተቀየመው። ምን መቀየም ብቻ… ከሀገር እንዲሰደድ ሁሉ አደረገው እንጂ! ይህ ግለሰብ… ከዚህ በፊት ሁለት ሽሙጣዊ መፅሐፍትን ያሳተመ ሲሆን “የአቤ ቶኪቻው ሽሙጦች” እና “ስላቆች” ይሰኛሉ። አሁንም ቢሆን የማይሆን ነገር ካየሁ ከማሽሟጠጥ አልመለስም የሚለው ይህ ስደተኛ… እነሆ በዚህ ብሎግ ላይ ደግሞ በሽሙጥ የአፃፃፍ ብልሃት ቢያንስ በሳምንት አንድ ግዜ ልከሰት ብሎ “ሀ” ብሏል።

11 responses »

  1. zerihun says:

    LMAO ! bravo Abe

  2. dtheactivist says:

    venus was seen everywhere in the world , who said it was only in addis

  3. በለው! says:

    ይህ በቃለ አጋኖ የተደገፈው የልማት ዕድገት በቬነስ ሲጎበኝ በዓለማችን የመጀመሪያው ክስተት ሲሆን የብሔር ብሔረሰቦች ሕዝቦች ህገ-መንግስት የመንቀሳቀስና የመዘዋወር መብት ፕላኔቶች ላይም ተፅኖ ሳያሳድር ያልተሸራረፈ ሙሉ መብት እንዳጎነፀፋቸው ትናንት በዚህ ህገ-መንግስት ተጨፍልቀው የተሰሩ ብሔሮች ብቻ ሳይሆኑ ቀድሞ በስም ኢንጂ በመልክ የማናውቃቸው ፕላኔቶች የራሳቸውን ጉዞ በራሳቸው ወጪ በመቻል በተናጠል የመሽከርከር እንደአስፈላጊነቱ የመጋጨትና የመሰባበር ሙሉ መብት ያለባት አዲሲቷ የሕዳሴ ‘በአብዮታዊ ዴሞክራሲ’ የተቦጠረች ሀገር ስትጎበኝ ደስታችን ወደር የለውም… ለመሆኑ ቬነስ በፌዴራሉ የከተማ ፀሐይ ሥር ስታልፍ…ከከተማው ሥር በውሃ ቦይ ውስጥ የሚኖሩት ህፃናት (የቀዳማዊት እመቤት ልጆች) የማየት ዕድሉ ነበራቸው?ወይንስ አልበሉም እና አንገታቸውን ቀና ማድረግ አልቻሉም ? ?

  4. aberha says:

    abe god bless you and you are really a true son of ethopia.

  5. Buta madingo says:

    Abe yemeche berta.

  6. Mesfin Getu says:

    Abe you made my day.

  7. Taddy Wedi says:

    Aba menew venusen baderegen yehen hule lemate lemayet.lol
    en endehon ye goregisen gidegeda tedegifa mayet tesenongal.

  8. ሽብር ሽብር ፧ ይላል ፡፡ says:

    ዘግይቶ የደረሰን ዜና ፡፡ ቬኑሰ የግንቦት አህያ ፡ ይቅርታ ግንቦት ሃያ ተብሎ ይነበብ ፡ ባህል እያከበርን ባለንበት ወቅት በአገራችን ማለፏ አንድ ፡ የግንቦት ሃያ ፍሬ ማሳያ ነች ሲሉ ፡ ዋልታ ያነጋገራቸው አንዳንድ ግለአቦች ገለጽ ፡፡ አክለወም ፈጣን እንደሚሳዬል ተምዘግዛጊ ልማታችን በዚ ከቀጠለ በየ አመቱ ፡ ሁሉም ፕላኔቶች በአገራችን እንደሚያልፉ ያላቸውን ተሰፋ ገልጸዋል ፡፡

  9. Ayichew says:

    እንዴት ደስ ይላል ምን ታድርግ ቬኑሰ በኢትዮጵያ እየተደረገ ያለውን ጉድ ሁሉም በዝምታ ሲያልፈው እሷ እንኳን ልታየው መጣቻ!!! በስደት፡ በችጋር፡ በግድያ፡ በዘረፋ፡ በእስራት፡ በእንግልት የሚማቅቀውን የኢትዮጵያ ህዝብ!!!! እናማ ለሰሚዎቹ ታደርስልን ዘንድ እንማጸናለን::

  10. ARADA says:

    Dear Abe,
    I enjoy all your books,article and so on. Since I heard that u r in exile I was saddened and need to contact u to express my support for u but for security reason it will be hard to find u but now I want to try as follow
    I know Samson (quatero) and he knows me very well. If u r happy tell him to sent me an email and we will start from there and I will be happy to contact u via Samson or directly. Till then keep safe.
    God bless you.

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s